ዝቅተኛ የፕሮቲን ይዘት ያላቸው ምግቦች መመገብ ለአዕምሮ ጤና እድገት ከፍተኛ ጠቀሜታ አለው

ዝቅተኛ የፕሮቲን ይዘትና  ከፍተኛ የካርቦሃይድሬት መጠን ያላቸውን ምግቦችን መመገብ ለአዕምሮ ጤና ዕድገት ከፍተኛ አስተዋፅዖ ያለው መሆኑ ተገለፀ።

ዝቅተኛ የፕሮቲን እና ከፍተኛ የካርቦሃይድሬት ይዘት ያላቸው ምግቦችን መመገብ ከአዕምሮ ጤና ዕድገት በተጨማሪም ረጅም ዕድሜ ለመኖር  የሚያስችል መሆኑን የሲድኒ ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎች ባካሄዱት ጥናት አረጋግጠዋል።

ተመራማሪዎቹ በጃፓንና በአንዳንድ የሜዲትራኒያን ሀገሮች በብዛት የተለመደው ይህ የአመጋገብ ስርዓት ለአዕምሮ ጤና ዕድገት ያለውን ጠቀሜታ ለማወቅ ጥናት አካሂደዋል።

ተመራማሪዎቹ ጥናታቸውን በቤተሙከራ ውስጥ በአይጦች ላይ ያደረጉ ሲሆን፥ በውጤቱም ዝቅተኛ ቅባት እና በምትኩ ከፍተኛ የካርቦሀይድሬት ይዘት ያላቸው ምግቦችን መመገብ ለአጠቃላይ ጤና መሻሻል ብሎም ለአእምሮ ጤና ዕድገት ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያለው መሆኑ ተረጋግጧል።

ይህም  በአሁኑ ወቅት ሁነኛ መድሀኒት ላልተገኘለት የአዕምሮ ህመም  እንደ ትልቅ መፍትሄ የሚታይ መሆኑን የጥናቱ መሪ ዴቪን ዋህል ተናግረዋል።

በመሆኑም በአሁኑ ወቅት የአብዛኛውን ቤት እያንኳኳ ያለውን የአዕምሮ ጤና ህመም ለመቀነስ የአመጋገብ ስርዓትን ማስተካከል  ተቀዳሚ ተግባር ሊሆን ይገባል ተብሏል።

በርግጥ በተለይም የምግብ አቅርቦት ችግር በሌለባቸው የአውሮፓ ሀገራት ላይ ይህን የአመጋገብ ስርዓት ለመተግበር አስቸጋሪ መሆኑን  ተመራማሪዎች ተናግረዋል።

ይህንን ሁኔታ ለመቀየርም  ዝቅተኛ የካሎሪ ይዘት ያላቸው ምግቦችን ማዘውተር የአእምሮ እድገትን በመጨመር ከፍተኛ የማስታወስ ችሎታ የሚያጎናፅፍ መሆኑን በመገንዘብ፥ የሚመለከታቸው ባለ ድርሻ አካለት ለማህበረሰቡ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራ መስራት እንዳለባቸው ተጠቁሟል።

ምንጭ: ኤፍ ቢ ሲ(FBC)

Advertisement

2 Comments

Comments are closed.