Sport News: በራሂም ስተርሊንግ ላይ የዘረኝነት ጥቃት ፈፀሟል የተባለው ግለሰብ የእስር ውሳኔ ተላለፈበት – Man Arrested After Alleged Racist Attack on Raheem

                                                   

በማንችስተር ሲቲ እና በእንግሊዝ ብሄራዊ ቡድን ተጫዋቹ ራሂም ስተርሊንግ ላይ የዘረኝነት ጥቃት ፈፅሟል የተባለው ግለሰብ በዛሬው ዕለት (ረቡዕ) ችሎት ፊት ቀርቦ የ16 ሳምንታት የእስር ውሳኔ ተላልፎበታል።

የ23 ዓመቱ ስተርሊንግ ማንችስተር ሲቲ ቅዳሜ ከቶተንሃም ጋር ከመጫወቱ በፊት ኢትሃድ የልምምድ ሜዳ እንደደረሰ በእግር የመረገጥና የዘረኝነት ጥቃት እንደተፈፀመበት ዘገባዎች አመልክተው ነበር።

የግሬተር ማንችስተር ፖሊስ እንደገለፀው ከሆነ የ29 ዓመቱ ካርል አንደርሰን የተሰኘ ግለሰብ በማንችስተር ከተማ ዉድዋርድ መንገድ ላይ ከመጠን ያለፈ ጥቃት ፈፅሟል በሚል ክስ አቅርቦበታል።

በዚሁ መሰረት የግለሰቡን ጥፋት በዛሬው ዕለት ሲመለከት የቆየው በማንችስተር ከተማ በሚገኘው ሳልፎርድ የንጉሳውያን ፍርድ ቤት ግለሰቡ ለ16 ሳምንታት ዘብጥያ እንዲወርድ ውሳኔ አስተላልፎበታል።

በልምምድ ሜዳው መግቢያ ላይ ድርጊቱ የተፈፅመው የተጫዋቹ ክለብ የሆነው ማንችስተር ሲቲ በጉዳዩ ላይ የሰጠው ይፋዊ አስተያየት የለም።

ነገር ግን በልምምድ ሜዳው ላይ በተገጠመው የደህንነት የቅኝት ካሜራ እይታ የተቀረፀ ሰፊ ሽፋን ያለው የቪዲዮ ምስል ለፓሊስ በማስረጃነት አቅርቧል።

ምንጭ:- ኢትዮአዲስ ስፖርት

Advertisement