የውልደት መጠን እጅጉኑ እየቀነሰ መሆኑ ታውቋል

 

ተመራማሪዎች እነሆ ‘ጉደኛ ወሬ’ ብለዋል፤ በዓለማችን የውልደት መጠን እጅግ በጣም እየመነመነ ነው። የት? ለምን? ትንታኔውን ለእኛ ተውት ይላሉ።
ተመራማሪዎቹ ጥናት ካደረጉባቸው ሃገራት ገሚሱ የውልደት መጠናቸው ከመቼውም ጊዜ በላይ ቀንሷል፤ ይህ ደግሞ የህዝብ ቁጥር ቀውስ ማምጣቱ አይቀሬ ነው።
አጥኚዎቹ ውጤቱን ‘አስደናቂ’ ብለውታል፤ ማንም አልጠበቀውምና።
ሌላው ውጤቱን አስደንጋጭ ያደረገው ነገር በእነዚህ ሃገራት መጭው ጊዜ በርካታ ወጣቶች ሳይሆን በቁጥር የበዙ አያቶች የምናይበት መሆኑ ነው።

ላንሴት የተባለ መጽሔት ላይ የወጣው መረጃ እንደሚጠቁመው በፈረንጆቹ 1950 የውልደት መጠን በአማካይ 4.7 የነበረ ሲሆን አሁን ግን ወደ 2.5 ወርዷል።
ወደ አፍሪቃ ስንመጣ ግን ነገሩ የተገላቢጦሽ ሆኖ እናገኘዋለን።
በምዕራብ አፍሪቃዋ ሃገር ኒጀር የውልደት መጠኑ 7.1 ነው፤ ወደ ቆጵሮስ ብናቀና ሴቶች በሕይወት ዘመናቸው በአማካይ የሚወልዱት አንድ ልጅ ነው።
ግን ግን. . .’ትክክለኛው’ የውልደት መጠን ስንት ነው?
አውነት እኮ ነው፤ ትክክለኛው የውልደት መጠን ስንት ነው? እርግጥ ስህተት የሆነ የውልደት መጠን አለ እያልን አይደለም፤ እንደው ተመካሪው ለማለት እንጂ።
በዚህ ጉዳይ ከእኛ በላይ ማን ሊቅ? የሚሉ ባለሙያዎች የውልደት መጠን ከ2.1 በታች የሆነ ጊዜ ‘ችግር አለ’ ይላሉ።
ጥናቱ የጀመረው በፈረንጆቹ 1950 ገደማ ነው፤ አዎ! የዛሬ 70 ዓመት አካባቢ። ለዚህ ነው ‘ኧረ ጎበዝ ጉደኛ ወሬ ይዘናል’ ብለው ብቅ ያሉት።
በፈረንጆቹ 1950 የውልደት መጠን በአማካይ 4.7 የነበረ ሲሆን አሁን ግን ወደ 2.5 ወርዷል
ከአጥኚዎቹ አንዱ የሆኑት ፕሮፌሰር ክርስቶፈር መሪ «አሁን የደረስንበት ደረጃ አንዳንድ ሃገራት ትውልድ መተካት የማይችለቡት ደረጃ ላይ መድሳቸውን ያመለክታል» ይላሉ።
«አስደናቂ እኮ ነው። ውጤቱ እኛ አጥኝዎችንም ጉድ በል. . .ያሰኘ ነው። በተለይ ደግሞ ከዓለም ህዝብ ግማሽ ያህሉ የትውልድ ቁጥር ማሽቆልቆል ሰለባ መሆኑ ዱብ ዕዳ ነው የሆነብን።»
ለመሆኑ ሃገራቱ እነማን ናቸው. . .?
ምጣኔ ሃብታቸው ጎልበቷል የተባለላቸው አውሮጳ ውስጥ ያሉ ሃገራት፤ አሜሪካ፤ ደቡብ ኮሪያና አውስትራሊያ የውልደት መጠናቸውን እያነሰ የመጡ ሃገራት ናቸው።
ልብ ይበሉ፤ የእነዚህ ሃገራት የህዝብ ቁጥር ቀንሷል ማለት ግን አይደለም፤ መሰል ለውጦችን ማየት ቢያንስ የትውልድ ልውውጥን ያህል ጊዜ ይወስዳልና።
«በቅርቡ የህዝብ ቁጥር ማሽቆልቆል እንደ አንድ ትልቅ ችግር ሲነሳ መስማታችን አይቀርም» ሲሉ ፕሮፌሰር መሪ ይተነብያሉ።
የማይካደው እውነታ ግማሽ ያህል የዓለም ሃገራት አሁንም ከፍተኛ የሆነ የውልደት መጠን አላቸው። ነገር ግን ዋናው ጉዳይ ወዲህ ነው፤ እኚህ ሃገራት በምጣኔ ሃብት እየጎለበቱ መምጣታቸው ስለማይቀር የውልደት ምጣኔያቸውን እየቀነሱ ይመጣሉ።
ለምን. . .?
አሁን ወደገለው እንግባ። ለምንድን ነው የውልደት መጠን እንዲህ ‘በአስደንጋጭ’ ሁኔታ የቀነሰው?
አጥኚዎቹ ሦስት ወሳኝ ነጥቦችን ያስቀምጣሉ።
ሴቶች ለመውለድ ያላቸው ፍላጎት መቀነሱ
የወሊድ መቆጣጠሪያ መላዎች በሽ መሆን
ከቀድሞ በላቀ ሴቶች ወደትምህርት ቤትና ሥራ መሄድ መቻላቸው
ከላይ የተጠቀሱትን ምክንያቶች ለተመለከተ ‘እና የውልደት መጠን መቀነሱ መልካም ዜና አይደል እንዴ?’ ሊል ይችላል፤ ስህተትም የለውም።
ሰዎች ከቦታ ቦታ የመዘዋወር ነፃነታቸው ካልተከበረ የዕድሜ መግፋትና የህዝብ ቁጥር ማሽቆልቆል የመጪው ጊዜ ራስምታቶች መሆናቸው ሳይታለም የተፈታ ነው።
የኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲው ዶ/ር ጆርጅ ለሰን ሰዎች ከለውጡ ጋር ራሳቸውን ማራመድ ከቻሉ ችግር አይሆንም ይላሉ።
ምሁሩ ንግግራቸው ጠጠር ያለ ይመስላል፤ የምሁር ነገር። ቀለል ባለ አማርኛ የሰዎች የመንቀሳቀስ ነፃነት ከተጠበቀና ከጊዜው ጋር መራመድ ከቻልን ማለታቸው ነው።
«ስነ-ህዝብ ሁሉንም የሚነካ ነው። እስቲ ወደ መስኮታችን ጠጋ ብለን ውጭውን እንመልከት። ሁሉም ነገር በፍጥነት ነው የሚንቀሳቀሰው፤ ግንባታው፣ መኪኖች፣ ትራፊኩ. . . ይህ ሁሉ ለውጥ የህዝብ ቁጥር መጨመር ያመጣው ነው። ከዚያም ባለፈ የዕድሜው ጉዳይም ትልቅ ተፅዕኖ አለው።»
ምሁሩ ሁሉም ነገር ይቀየራል፤ መቀየሩም ግድ ነው ይላሉ። የስራ ቦታዎች መቀየር አለባቸው፤ የጡረታ ጊዜውንም አስቡበት (ይጨመር ማለታቸው ነው) ይላሉ ዶ/ር ለሰን።
«ጃፖኖችን ተመልከቱ፤ ዕድሜው የሄደ ትውልድ ስጋት ይዟቸዋል። ወደምዕራብ ስትመጡ ግን ወደሃገራቱ የሌላ ሃገር ዜጎች ስለሚገቡ ይህ ስጋት ብዙ አይታይም።»
ምንም እንኳ መሰል ለውጦችን መቀበል ቀላል ባይሆንም ጥቅሙ የላቀ ስለሚሆን መቀበል አዋጭ ነው፤ የምሁሩ ሃሳብ ነው።
ቻይናም በ1950 ከነበራት ግማሽ ቢሊየን ህዝብ ወደ 1.5 ቢሊየን ደርሳለች፤ በአንድ ልጅ ፖሊሲ በመታገዝ።
የአንድ ልጅ ፖሊሲ ጉዳይ አዋጭ መስሎ ያልታያት ቻይናም ‘ፖሊሲው በቃኝ’ ብላለች፤ መቼም አርጀት ካለው ጎረምሳው ይሻለኛል በማለት።
ወጣም ወረደ የዓለም ህዝብ ተጋግዞ ለችግሩ መላ ካላበጀለት መፃኢያችን በችግር የተተበተበ ነው። ቁምነገሩን በልባችን ያፅናልን!!!

ምንጭ: ቢቢሲ

Advertisement

3 Comments

Comments are closed.