በአፍ የሚወሰዱ የፀረ-ኤች አይ ቪ መድሃኒቶች በመርፌ ሊቀየሩ እንደሚችሉ ተመራማሪዎች ገለፁ::

                                                

በአፍ የሚወሰዱ የፀረ ኤች አይቪ መድሃኒቶች በመርፌ ሊቀየሩ እንደሚችሉ ተመራማሪዎች ጠቁመዋል፡፡

የኤች አይ ቪ ተጠቂዎቹ በመርፌ የሚሰጡ መድሃኒቶችን በዓመት ስድስት ጊዜ ብቻ እንዲወስዱ ለማድረግም ታልሟል፡፡

በመርፌ ለመስጠት የተቀመሙት የፀረ-ኤች አይ ቪ መድሃኒቶች በአፍ ከሚሰጡት የተሻለ በሽታውን የመግታት አቅም እንደሚኖራቸውም ነው የተነገረው፡፡

የኤች አይ ቪ ኤድስ ህሙማን ካቦቴግሬቪር እና ሪልፒቫይሪን የተባሉ መድሃኒቶችን በየአራት ወይም በየስምንት ሳምንት እንዲወስዱ የማድረግ እቅድም መኖሩን ተመራማሪዎቹ ጠቁመዋል፡፡

እነኝህ ሁለቱ መድሃኒቶች አሁን በአፍ ከሚወሰዱት እንክብሎች በተሻለ ሁኔታ ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ ለሚኖርባቸው ሰዎች ምቹ እንደሚሆኑ ተጠቁሟል፡፡

በርካታ ሰዎች በየቀኑ የሚወሰዱትን የፀረ ኤች አይቪ መድሃኒቶች አላምጦ ለመውሰድ ሲቸገሩ ይስተዋላል።

የመድሃኒቶቹ ቀማሚዎች ከሆኑት መካከል ዶክተር ዴቪድ ማርጎሊስ እንደተናገሩት ላለፉት አስርት ዓመታት ለተጠቂዎቹ ምቹ የሆነ የመድሃኒት ዓይነት ለማዘጋጀት ጥረት አድርገዋል፡፡

በጆርናል ኦፍ ላሴት ላይ የሰፈረው የጥናት ውጤት በፓሪስ በሚካሄደው ዓለም አቀፉ የኤድስ ማህበረሰብ ጉባኤ ላይ በይፋ ሙከራ እንደሚደረግለት ታውቋል፡፡

በጥናቱ ውስጥ የተካተቱ በ286 ህሙማን የካቦቴግሬቪር እና የሪልፒቫይሪን መድሃኒቶችን ከፊሎቹ በየቀኑ በአፋቸው እንዲወስዱ፣ የተወሰኑት በመርፌ አማካኝነት በየወሩ እንዲወስዱ ከፊሎቹ ደግሞ በየሁለት ወሩ በመርፌ እየተወጉ እንዲጠቀሙ ተደርጓል።

ከ32 ሳምንታት ክትትል በኋላም በሽታው በደም ውስጥ ያለው ስርጭት በየቀኑ በእንክብል መልክ በሚወስዱት ላይ 91 በመቶ ሆኖ ተገኝቷል።

በየወሩ የወሰዱት ደግሞ 94 በመቶ ሲሆን በየሁለት ወሩ የወሰዱት 95 በመቶ በሽታው ሊመጣ የሚችለውን መጠነ ሰፊ ጉዳት ቀንሶላቸው ተገኝቷል፡፡

በአሁኑ ወቅት በዓለም ላይ 37 ሚሊየን ሰዎች በኤች አይ ቬ ኤድስ ተጠቅተዋል። 

ምንጭ:- ኤፍ ቢ ሲ(FBC)

Advertisement