‹‹ካላዛር 46 አይነት የበሽታ ዝርያዎች አሉት፡፡ ካላዛር በህክምና ይድናል፤ በወቅቱ ህክምና ካላገኘ ደግሞ ገዳይ በሽታ ነው፡፡›› የጤና ባለሙያዎች

ሻምበል ወርቁ

በወቅቱም የካላዛር በሽታ በርሃ ቀመስ በሆኑ የሀገራችን አካባቢዎች ‹‹የአሽዋ ዝንብ›› በምትባል ትንኝ አማካኝነት የበሽታው ተህዋሲያን በሰዎች ላይ እንደሚከሰት እውቅና ተፈጠረ፡፡ ካላዛር 46 አይነት ዝርያዎች እንዳሉትም ታወቀ፡፡ 
ከ1996 ዓ.ም ጀምሮም በተለይም በደቡብ ጎንደር ዞን ሊቦ ከምከም ወረዳ አካባቢ በሽታው በርካታ የህብረተሰብ ክፍሎችን ያጠቃ ስለነበር ህክምናውን በነፃ መሰጠት እንደ ተጀመረ በአዲስ ዘመን የመጀመሪያ ሆስፒታል ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡

የካላዛር በሽታ ቀደም ብሎ በአዲስ ዘመን ከተማ ጤና አጠባበቅ ጣቢያ እና አሁን ደግሞ በአዲስ ዘመን የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ብቻ እንደሚሰጥ ቢታወቅም አልፎ አልፎ ህሙማኑ ለተጨማሪ ህክምና ወደ ጎንደር ሆስፒታል ይላካሉ ሲባል ሰማንና ምክንያቱ ምን ይሆን? ስንል የሆስፒታሉን የጤና ባለሙያዎች ጠይቀን ነበር፡፡

ካላዛር በህብረተሰቡ ዘንድ ያለው እውቅና አናሳ በመሆኑ ህሙማኑ ወደ ሆስፒታላችን ሲመጡ በከፍተኛ ሁኔታ ተጎድተው ነው የሚመጡት የሚሉት በአዲስ ዘመን የመጀመሪያ ሆስፒታል የላብራቶሪ ባለሙያው አቶ እንዳልክ ጥላሁን ሌሎች ተደራራቢ የጤና ችግሮች እንዳይኖሩባቸው በመስጋት አልፎ አልፎ ወደ ጎንደር ሪፈራል ሆስፒታል ለተጨማሪ ምርመራ የሚላኩበት ጊዜ እንዳለ ገልፀውልናል፡፡

አልፎ አልፎም የመመርመሪያ መሳሪያዎች አገልገሎት የሚቋረጥበት ሁኔታ ያጋጥማል የሚሉት ባለሙያው በእንደዚህ ያሉ አጋጣሚዎች ለተጨማሪ ምርመራ የምንልካቸው ህሙማን ይኖራሉ፡፡ ነገር ግን አሁን ባለው ነባራዊ ሁኔታ ሆስፒታሉ የካላዛር በሽታን ለመመርመር እና የህክምና ድጋፍ ለማድረግ የሰለጠነ የሰው ኃይልም ሆነ የመድሃኒት አቅርቦት ችግሮች የሉበትም ብለውናል፡፡

በአዲስ ዘመን የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል የካላዛር ህሙማን ክፍል ውስጥ ያገኘናቸው ታካሚ ንጉሴ መኳንንት እና ጌትነት ታደሰም ያረጋገጡልን ሆስፒታሉ በቂ ክትትል እና ድጋፍ እያደረገላቸው መሆኑን ነው፡፡

የበሽታው ተህዋሲያን ተሸካሚ የሆነችው ትንኝ በምትራባበት አካባቢ በሽታው በትንኟ አማካኝነት ከሰው ወደ ሰው ይተላለፋል የሚሉት የጤና ባለሙያዎቹ በተለይም በምሽት አጎበር እንዲጠቀሙ እና ተሸፋፍነው መተኛት እንዳለባቸው ይመክራሉ፡፡

የምግብ ፍላጎትና የክብደት መቀነስ፣ ነስር፣ በሆድ አካባቢ እብጠት እና ከሁለት ሳምንታት በላይ የዘለቀ ትኩሳት የካላዛር በሽታ ምልክቶች እንደሆኑ የሚናገሩት የጤና ባለሙያዎቹ በበርሃ አካባቢ እየተንቀሳቀሱ የሚሰሩ ሰዎች ወደ መኖሪያ አካባቢያቸው ከመመለሳቸው በፊት የካላዛር ምርመራ ሊያደርጉ ይገባል ነው ያሉት፡፡ 

ምንጭ:  Amhara Mass Media Agency

Advertisement

2 Comments

Comments are closed.