ልደቱ አያሌው:- ”ወደ ፖለቲካ ትግሉ ልንመጣ የምንችለው ያፈረሰን የምርጫ ቦርድ እራሱ ከፈረሰ ብቻ ነው”

የኢዴፓ የቀድሞ ሊቀመንበር አቶ ልደቱ አያሌው ማስፈራሪያም እየደረሰብኝ በመሆኑ ከፖለቲካ ሕይወት ወጥቻለሁ ማለታቸውን ተከትሎ ብዙ ሰዎች አስተያየታቸውን እየሰጡ ነው። ከዚህ ጉዳይ ጋር በተያያዘ የቢቢሲ አማርኛ ባልደረባ ቃልኪዳን ይበልጣል አንኳር ጥያቄዎችን አንስቶላቸው ነበር።

“በደጉ ጊዜ” ከፖለቲካው ራስን ማግለል ለምን?

አገር ውስጥ መንግሥትን በሰላማዊ መንገድ የሚገዳደሩ ፓርቲዎች ይቅርና ጎረቤት አገር ተጠልለው፣ ነፍጥ አንግበው ሲታገሉ የነበሩ ወደ አገር ቤት በሚገቡበት ወቅት አቶ ልደቱ ከዚህ ውሳኔ ለምን ደረሱ? ይህ ብዙዎች ሲያነሱት የነበረ ቁልፍ ጥያቄ ነው።

አቶ ልደቱ ይህንኑ አንጻራዊ መሻሻል ያለበትን የፖለቲካ አውድ ባያብሉም ለምን ራሳቸውን በዚህ ጊዜ ማግለል እንደፈለጉ የተብራራ መልስ አይሰጡም። እንዲያውም በዚህ መልካም ጊዜ ፓርቲያቸው በምርጫ ቦርድ እንዲፈርስ መደረጉ እንዳሳዘናቸው ይገልጻሉ።

በሃገሪቱ የተከሰቱት ቀውሶችና አዲስ አበባ

• ዐብይ አሕመድ ለኖቤል ታጭተዋል?

• ሰመጉ በወልዲያ እና አካባቢው የመብት ጥሰት ተፈጽሟል አለ

“ፓርቲ ከሌለኝ በግለሰብ ደረጃ የማደርገው ተሳትፎ ብዙም ጥቅም ይኖረዋል ብዬ አላስብም” በማለት ለምን በግላቸው ይህን ውሳኔ ለመውሰድ እንደበቁ ለማስረዳት ይንደረደራሉ።

መቀሌ ተዘጋጅቶ በነበረ ጉባኤ መሳተፋቸው ያላስደሰታቸው ወገኖች ዛቻና ማስፈራሪያ እንዳደረሱባቸውና ይህም ለውሳኔ እንዳበቃቸው ለቢቢሲ ተናግረዋል።

“…ለምን መቀሌ ሄዶ ስብሰባ ተካፈለ ብለው ከፍተኛ የሆነ የስም ማጥፋት ዘመቻ ከፍተውብኝ፤ እንገድልሃለን፤ ንብረትሀን እናቃጥላለን የሚሉ መልእክቶች እደረሱኝ ነው።” ብለዋል።

በድርጅት ደረጃ የሚያደርጉት አስተዋጽኦ እስከሌለ ድረስ፤ ነጻ ሐሳባቸውን ለመግለጽ በመሞከራቸው ብቻ እንደዚህ ዓይነት ለሕይወት የሚያሰጋ ማስፈራራት የሚደርስባቸው ከሆነ፤ “ነገሮች ትንሽ እስኪሰክኑ ድረስ ከየትኛውም ዓይነት የፖለቲካ ተሳትፎ ራሴን መቆጠብ አስፈላጊ ሆኖ አግኝቼዋለው” ሲሉ ራሳቸውን ከፖለቲካ ያገለሉበትን ምክንያት ለቢቢሲ ጨምረው አስረድተዋል።

“ፖለቲካ ነፍሴ ደስ ብሏት የማካሄደው ሥራ ነው”

ያም ሆኖ አቶ ልደቱ ብዙዎቹ እንደጠረጠሩት እስከወዲኛው ራሳቸውን ከፖለቲካ ያገለሉ አይመስልም። ከቢቢሲ ጋር በነበራቸው ቆይታ “ሁኔታዎች ከተለወጡ” ወደ ፖለቲካው እንደሚመለሱ ፍንጭ ሰጥተዋል።

”…ከፖለቲካ ለዘልዓለም እወጣለው ማለት አይደለም። ፖለቲካ በጣም ነው የምወደው፤ ፈልጌ ነብሴ ደስ ብሏት የማካሂደው ሥራ ነው። ስለዚህ በሕይወቴ ከፖለቲካ እወጣለው ብዬ አላስብም።”

• በጂግጂጋ የህክምና ቁሳቁሶች እጥረት አሳሳቢ ሆኗል

• ፓርላማው የኦነግ፣ ኦብነግና ግንቦት 7 የሽብርተኝነት ፍረጃ መነሳትን አፀደቀ

ይህ በግል ለፖለቲካ ተሳትፏዋቸው የሰጡት የ “እመለስ ይሆናል” ፍንጭ ነው። እንደ ድርጅት ወደ ፖለቲካ ለመመለስ ግን አንድ ቁርጥ ቅድመ ሁኔታን አስቀምጠዋል፤ ምርጫ ቦርድ ፈርሶ መሠራት እንዳለበት።

“ወደ ፖለቲካ ትግሉ ልንመጣ የምንችለው ያፈረሰን የምርጫ ቦርድ እራሱ ከፈረሰ ብቻ ነው”

ኢዴፓን ማን አፈረሰ?

ኢዴፓን ለማፍረስ 1 ዓመት ከ8 ወር የፈጀ ጥረት ተደርጎ ነበር የሚሉት አቶ ልደቱ ይህንንም ጥረት ለማክሸፍ ከፍተኛ ትግል ውስጥ እንደነበሩ ተናግረዋል። “አምስት ጊዜ ሙከራ የተደረገብን ሲሆን፤ አምስቱንም ማክሸፍ ችለናል።” ይላሉ።

ፖርቲያቸውን በማፍረሱ ሂደት የምርጫ ቦርድን ተሳትፎ ሲያጎሉም ከፖርቲያቸው በሐሳብ ተሸንፈው የወጡ ሰዎችን ጭምር በመያዝ ሸፍጥ እንደተፈጸመባቸው ያብራራሉ።

እነዚህን ሰዎች የሐሰት ክስ ፍርድ ቤት እንዲያቀርቡ በማድረግ፤ ምርጫ ራሱ ምስክር በመሆን ፍርድ ቤት እየቀረበ፤ ደብዳቤ እየጻፈ፣ “ፓርቲውን ከሕዝብ ወደ ግለሰብ እንድናስረክበው አድርጎናል” ሲሉ ምርጫ ቦርድን ክፉኛ ይተቻሉ።

አቶ ልደቱ ምርጫ ቦርድ ጣልቃ ገብቶ ፓርቲውን ያፈረሰው ስለመሆኑም በቂ መረጃ አጠራቅመው መያዛቸውን፣ ይህንን ሰነድም ለጋዜጠኞች ማሳየት እንደሚችሉ ተናግረዋል።

“እንደማልፈራማ የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚያውቅ ይመስለኛል”

ከፖለቲካ ራሳቸውን የማግለል ውሳኔ የወሰኑት አቶ ልደቱ እንዴት በዛቻ ምክንያት ራሳቸውን አገለሉ የሚለው ነጥብ የርሳቸውን የፖለቲካ ጉዞ በሚከታተሉት ሁሉ የሚዋልል ጥያቄ ነው።

• ኦነግ ጊዜያዊ ተኩስ አቁም ማወጁን ገለፀ

• «የሠራዊታችን አባላት በክብር ይሸኛሉ» ግንቦት 7

“ማስፈራራትና ዛቻ ፈርቼ አይደለም ይህን የወሰንኩት” ያሉት አቶ ልደቱ “እንደማልፈራማ የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚያውቅ ይመስለኛል” ይላሉ፤ ከዚህ የከፉ ሁኔታዎች ማሳለፋቸውን በማውሳት። ይህን ካሉ ዘንድ እንዴት በዛቻና ማስፈራሪያ የፖለቲካ ማራቶንን ለማቋረጥ ወሰኑ?

“ከፖለቲካ ውጪ ሆኜ የምኖር ዓይነት ሰው አይደለሁም።”

”በመጀመሪያ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ትግል የሚባለውን ነገር እስከ መጨረሻው አላቋርጥም።” ያሉት አቶ ልደቱ “ከፖለቲካ ውጪ ሆኜ የምኖር ዓይነት ሰው አይደለሁም።” ይላሉ።

የፖለቲካ ግባቸውን ሲጠየቁም ”ለሕዝብ ወይም ለሃገር ብዬ ነው ፖለቲካን የማራምደው ብዬም አልመጻደቅም።እንደዚያ ብዬም አላውቅም” ካሉ በኋላ፣ “ፖለቲካን የማካሂደው ለማንም ብዬ ሳይሆን ለራሴ ብዬ ነው” ይላሉ።

“የኢዴፓ አጀንዳዎች ወደ ቤተ መንግሥት ገብተዋል”

አቶ ልደቱ የፖለቲካ ስኬትን ሥልጣን በመጨበጥ ብቻ እንደማይለኩት፣ ከዚያ ይልቅ የፖለቲካ ባሕልን በመቀየር ረገድ እንደሚመለከቱት ያትታሉ። ከዚህ አንጻር ፓርቲያቸው በርካታ ውጤቶችን እንዳስመዘገበም ያምናሉ።

ለዚህ እምነታቸው በዓመታት ውስጥ ሲታገሉላቸው የነበሩና ውግዘትን ያስከተሉባቸው ጉዳዮች አሁን የሕዝብ መሆናቸውን እንደ ማስረጃ ያቀርባሉ።

ለምሳሌ “ኢህአዴግን የችግሩ አካል ብቻ ሳይሆን የመፍትሄውም አካል አድርገን መሥራት አለብን” ብለው ገና ድሮ መነሳታቸውን ያስታወሱት አቶ ልደቱ ያን በማለታቸው በጊዜው ከፍተኛ ተቃውሞ እንዲደርስባቸው ማድረሱን ያስታውሳሉ።

“አሁን ግን ሕዝቡ ይህንን ሐሳብ ተቀብሎ ከጠቅላይ ሚኒስተር ዐብይ አሕመድ ጎን ሲቆምና ከኢህአዴግ መፍትሄ ሲጠብቅ ማየት ለኛ ትልቅ ድል ነው።”

ይህ ብቻም ሳይሆን ገዢው ፓርቲም ቢሆን የኢዴፓን አጀንዳዎች ወስዶ በመጠቀሙ ትግላቸው ፍሬ ማፍራቱን ይከራከራሉ።

”…አሁን ደግሞ ኢህአዴግ የፖለቲካ አጀንዳችንን እወሰደ ነው።…በእኔ እምነት አብዛኛዎቹ የኢዴፓ አጀንዳዎች ቤተ መንግሥት ገብተዋል።”

Advertisement

1 Comment

Comments are closed.